“ስለማንነቴ የነገርኩሽን ጊዜ ስታስታውሺ የሚመጣልሽ ሃሳብ ምንድነው?” ብዬ ስለኩዊርነት ለብዙ ጊዜ ለምታውቀው የእህቴ ልጅ የፅሁፍ መልዕክት ላኩላት::
“እ እኔንጃ… የመቀራረብ ስሜት ፈጥሮብኛል..ይበልጥ ያቀረበኝ ይመስለኛል:: ትንሽ ደንግጫለሁ ግን በመጥፎ አይደለም..” መለሰችልኝ:: ቀላል የሚመስል ነገር ግን በጣም ጥልቅ ምላሽ ስለሆነ “እኔንጃ” ብላ ያሳጠረችውን ራሱ አልፌያታለሁ::
ግልፅ መሆን ለቤተሰብ መቀራረብ ወሳኝ ሲሆን የኔ ግልፅ መሆን ደግሞ የነበረን ግንኙነት ላይ ይበልጥ እንድንቀራረብ አድርጎናል:: ይሄን የፅሁፍ መልዕክት ያስታወሰኝ ከህብስት ጋር ራስን በመሆን እና ማወቅ ዙሪያ በነበረኝ የዚህ ወር ፖድካስት ውይይት ነው::
ተመሳሳይ ፃታ አፍቃሪ ጠል እንድንሆን ተደርገናል ነገር ግን ቤተሰቦቿ ከዚሁ የተመሳሳይ ፃታ አፍቃሪ ጠል ማህበረሰብ ውጤት ቢሆኑም ራሷን መሆን እንድትችል ማድረጋቸው ተስፋን ይሰጣል:: ሃይማኖት፣ ወግ አጥባቂነት፣ ብሄራዊ ስሜት፣ ሳይንሳዊ ያልሆኑ ትርክቶች እና LGBTQ+ የውጭ ተፅዕኖ ነው የሚል ስሜት ኢትዮጵያ ስርዓተ ፃታንና ወሲባዊነትን እንደ አንድ ክፍል እንዳታይ የሚያደርጉ እንቅፋቶች ናቸው::
“ራስ ወዳድ ሁኑ” ትላለች ህብስት ስለራስን መቀበል እና እውነተኛ ህይወትን መኖር አስፈላጊነት ስትገልፅ:: ቀጥላም ስሜቶቻችን ስህተት ሊሆኑ እንደማይችሉና ማብራሪያም ሆነ ማሳመኛ እንደማያስፈልገው ገልፃለች:: ራሷን እንደፓንሴህሽዋል መረዳትና መቀበል መቻሏ ራሷን ከመቀበል በፊት ከነበረው ህይወት በሚፃረር መልኩ የህይወት ድምቀትን ሰጥቷታል:: የምትራመደው የህይወት መንገዷ የሰላም ስሜትና ቅለትን የፈጠረው ራሷን መቀበል በመቻሏ ነው::
ራስን ማወቅ እና መኖር ትልቅ ፈተና ነው፤ የማያልቅም ሂደት ነው:: የህብስት የህይወት ልምድ ገለፃ ተመሳሳይ ፃታ አፍቃሪ ጠል በሆነ ማህበረሰብ ውስጥ ስንኖር ለራሳችን ደግ እንድንሆን ያስታውሰናል:: ይበልጥ ግን ማንነታችንን ስንቀበል የሚቻለውን ስዕል ስላልናለች፤ ህይወታችንን አርነት በሚያወጣ መንገድ እውነተኝነት እና ነፃነት::