
በኢትዮጵያ የጸጥታ አካሎች ግለሰቡን “ሴት እንደሆነ በማስመሰል” ወንጀል ባለፈው አመት ውስጥ ሶስት ጊዜ በቁጥጥር ስር አውለዋል። ልቤ ለእሳቸው (ይህንን ተውላጠ ስም እየተጠቀምኩበት ስለ ተመራጭ ተውላጠ ስም እርግጠኛ ስላልሆንኩ ነው) በጣም አዘነ። እራሳቸውን በዚህ መንገድ ማቅረባቸው ለከፍተኛ ምርመራ እና ህመም ዳርጓቸዋል። ወደ ፖሊስ ጣቢያ የመወሰድ ገጠመኝ ምን ያህል አስፈሪ ሊሆን እንደሚችል መገመት አልችልም እንዲሁም በዚያ በሚቆዩበት ጊዜ በደል የሚደርስባቸው መንገዶች። ፎቶአቸውን ከተሰበሰቡ የፖሊስ አባላት ጋር ባየሁ ቁጥር የፍርሃት ማዕበል እና አቅመ ቢስነት ይሰማኛል። ስለ ደህንነታቸው እና በአእምሮ ጤንነታቸው ላይ የሚደርሰው ጉዳትን ሳስብ በጥልቅ እጨነቃለሁ።
የዚህኛውን ጊዜ እስራቸውን አንድ ወዳጄ በፌስቡክ ላይ ፖስት የተደረገውን ዜና ሲያካፍልኝ በሆዴ ውስጥ የፍርሃት ቋጠሮ ተሰማኝ። ከዜናው አንባቢያን የሚሰነዘሩት አስተያየቶቹ ያው ከእንደዚህ አይነት ነገሮች ጋር ተያይዞ የተለመደውን የስድብ ናዳና የግድያ ዛቻዎችን ጠብቄ ነበር። ነገር ግን በተቃራኒው ሚዛናዊ የሆነ ውይይት በማግኘቴ በጣም ተገረምኩ። አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ግለሰቡ መተው እንዳለባቸው አጥብቀው ተከራክረዋል። ማንኛውም ሰው ህብረተሰቡ ምንም ይሁን ምን እራሳቸውን እንደ ምርጫቸው የማቅረብ መብት እንዳላቸው በአጽንኦት አስተያየት ሰጥተዋል። ሌሎች ደግሞ እኚህ ሰው ርህራሄ እና ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው እንጂ በማንነታቸው እንደ ወንጀለኛ መቆጠር የለባቸውም ብለው አጥብቀው ፅፈዋል። በተለይ ልቤን የነካኝ አስተያየት ደግሞ በሙሉ ነፃነት የመኖር መብት እናዳላቸው የተከራከረው ነው፣ ይህም በግለሰብ መብቶች ላይ እየጨመረ ያለውን ግንዛቤ አጉልቶ ያሳያል።
እንደ አለመታደል ሆኖ የተለመዱ ስድቦች እና አሉታዊ አስተያየቶች ቢኖሩም፣ የአንድነት እና የድጋፍ መልእክቶችን መመልከቱ በጣም አስደሳች ነበር። ብዙ ግለሰቦች ርኅራኄን እና ተቀባይነትን ለማስፋፋት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል፤ ይህም በህብረተሰቡ ውስጥ የአስተሳሰብ ለውጥ ሊኖር እንደሚችል ያሳያል። የዚህ ዓይነቱ ውይይት ወሳኝ ነው ጎጂ አመለካከቶችን የሚፈታተን እና የበለጠ አካታች አካባቢን የሚያጎለብት አካሄድ ሊፈጥር ይችላል።
እኚህ ሰው በማንነታቸው ብቻ ወደ ፖሊስ ጣቢያ የሚጎተቱበት ይህ የመጨረሻ ጊዜ እንደሆነ ከልቤ ተስፋ አደርጋለሁ። የእንደዚህ አይነት ገጠመኞች ስሜታዊ እና ስነ ልቦናዊ ጉዳት እጅግ በጣም ብዙ እንደሆነ አያጠራጥርም፣ እና ማንም ሰው እውነተኛ ህይወቱን እና ማንነቱን ለመኖር እንደዚህ አይነት ፍርሃት እና ጭንቀት ውስጥ መኖር የለበትም። እንዲሁም አዎንታዊ አስተያየቶቹ ማህበረሰቡ ውስጥ ተቀባይነት እና ግንዛቤ ቀስ እያለም ቢሆን እየተሰራጨ እንደሆነ የሚጠቁሙ በመሆናቸው ተስፋፍተው እንደሚቀጥሉ ተስፋ አደርጋለሁ። እነዚህ ለውጦች ቀስ በቀስ የሚመጡ ሊሆኑ ቢችሉም፣ ወደፊት ለበለጠ ጉልህ ለውጦች ተስፋ ይሰጡኛል፣ ይህም ሁሉም ሰው መድልዎ እና ስደት ሳይፈራ በነጻነት ወደሚኖርበት አገር እና ዓለም ያመራል።


