ኢትዮጵያ ውስጥ እንዳሉት አብዛኞቹ ቤተሰቦች፣ ሁሉም ወንድሞቼ እና እህቶቼ የትዳር ጓደኞቻቸውን ለበዓል ይዘው ይመጣሉ። እኔ ግን ለበዓል ማንንም ፍቅረኛ ቤት አምጥቼ አላውቅም። የረጅም ጊዜ ግንኙነት ውስጥ በነበርኩበት ጊዜም እንኳን ሁሌም በዓላቱን ለየብቻ እናሳልፍ ነበር፣ ማታ ላይ በዓሉ ካለፈ በኋላ እንገናኛለን።

እንድትረዱኝ ያህል ቤተሰቤ ሁልጊዜም እንደ ኩዊር እህታቸው በሚያስደንቅ ሁኔታ ይቀበሉኛል። እኔ እንደተወደድኩ እና እንደተቀበሉኝ እንዳውቅ አስተማማኝ ቦታ ፈጥረዋል። ነገር ግን በሆነ ምክንያት፣ በበዓላት ወቅት የእኔን የህይወት አጋር ለእነሱ ለማስተዋወቅ አስቤ አላውቅም። አውቃለሁ ይሄ እንደሚገርም። ምናልባት እስካሁን ሙሉ በሙሉ ያላስታረቅኩት አንዳንድ ስር የሰደደ የኩዊርነት የውስጥ ጥላቻ ምክንያት ሊሆን ይችላል። ወይም ደግሞ እኔና የትዳር ጓደኛዬ ልጅ ስለሌለን ወይም እንደ ተቃራኒ ፆታ አፍቃሪ ጥንዶች በይፋ “በጋብቻ” ስላልተሳሰርን ሊሆን ይችላል።
ነገር ግን በቅርቡ፣ ፍቅረኛዬ ለበዓል ወደ ቤተሰቤ ቤት እንድጋብዛት በእርጋታ አነሳሳችኝ። እርስ በርሳችን ቤተሰብ ውስጥ መካተታችንም ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ እንድገነዘብ አድርጋኛለች። እና ይህም አቋሟ ውሳኔ እንድወስድ አገዘኝ። እናም ጣፋጭ ኬክ ይዘን ወደ እናቷ ቤት ሄድን ከዛም ለእናቴ ኬክና አረቂ ይዛ ወደ ቤተሰቤ ቤት መጣች። አረቂዋ እናቴ ከእሷ ጋር በፍቅር እንደምትወድቅ አረጋግጣለች።
ሆኖም፣ ባልተጠበቁ ሁኔታዎች ምክንያት፣ ፍቅረኛዬ ከተጠበቀው በላይ ትንሽ ዘግይታ ደረሰች። ስትገባ ትንሽ የመረበሽ እና የተስፋ ድብልቅልቅ ተሰማኝ። እህቴ፣ እናቴ እና የአክስቴ ልጅ በቦታው ነበሩ። የመላው ቤተሰብ ስብስብ አልነበረም፣ ግን ይሄም በራሱ ትልቅ እርምጃ ነበር።
በጣም የገረመኝ እና ያስደስተኝ እህቴ፣ እናቴ እና የአክስቴ ልጅ ልክ እንደሌሎች የወንድሞቼ እና እህቶቼ የፍቅር አጋሮች እጆቻቸውን ዘርግተው ተቀበሏት። አብረን ሳቅን፣ አወራን እና ተጫወትን። በጣም ቆንጆ ጊዜ ነበር፣ እንዲሁም ለወደፊት በጣም ተስፋ የሚሰጥ ግንኙነት ነበር።
የፍቅረኛዬ መዘግየት ልታገኛችው የምትችለውን የቤተሰብ ቁጥርን እንኳን ቢቀንሰውም መምጣቷ የቁርጠኝነቷን ጥልቀት እና የሁለታችን በእያንዳንዳችን ቤተሰብ አባል ለመሆን ያለንን የጋራ ፍላጎት አሳይቶኛል። የእርሷ መገኘት ምንም እንኳን የህብረተሰብ እና የባህል ጫና ቢኖርም ነገሮች መሻሻል እንደሚችሉ አስታወሰኝ። አንድ ቀን ህይወታችንን ሙሉ በሙሉ ማዋሃድ እና ፍቅራችንን ለሁሉም የቤተሰባችን አባላት በግልፅ እንደምናካፍል ተስፋ ሰጠኝ። ለዚህም አመስጋኝ ነኝ።
ምክንያቱም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊት ኩዊር፣ የህይወት አጋሬን ወደ ቤተሰብ ስብስብ የማምጣት ሀሳብ በጣም ከባድ ሊሆን ይችላል። የበለጠ ፈታኝ ሊያደርጉት የሚችሉት ሃይማኖታዊ፣ ባህላዊ እና ማህበረሰባዊ ምክንያቶች አሉ። ለምሳሌ የእናቴ ሁኔታ ይህ ነበር፣ ለዛም ነው ፍቅረኛዬን እንደ ፍቅረኛ በግልፅ ያላስተዋወቅኩት።
ነገር ግን፣ እነዚህ ውስብስብ ነገሮች ቢኖሩም፣ ቤተሰቦቼ እንደ የፍቅር ጥንዶች ቦታ ለመስጠት ስላሳዩን አመስጋኝ ነኝ እናም ኩራት ይሰማኛል። በሁሉም ንግግሮች ውስጥ በግልፅ ባይታወቅም የግንኙነታችንን አስፈላጊነት ተገንዝበው ነበር። የእነሱ ተቀባይነት እና ድጋፍ ለእኛ ዓለም ትርጉም ነበረው ፣ እናም የእነርሱ ፍቅር እና ግልፅ ልባቸው ምስክር ነው።
ተቀባይነት ለማግኘት አስቸጋሪ በሆነበት ዓለም፣ ከመደበኛው ውጪ የሆኑ ማንነቶች እና ግንኙነቶች በተገለሉበት፣ የሚያቅፈን ቤተሰብ ማግኘታችን ታላቅ በረከት ነው። ፍቅር ድንበር እንደማያውቅ እና ማንነታችን እና የምንወዳቸው ሰዎች ክብር እና ተቀባይነት እንደሚገባቸው ማስታወሻ ነው።
ስለዚህ፣ በዚህ ልዩ የትንሳኤ ስብሰባ ላይ ሳሰላስል፣ ለቤተሰቤ ጥልቅ የሆነ የአድናቆት እና የፍቅር ስሜት አምጥቶብኛል። አንዳንድ የማንነታችን ገፅታዎች ሙሉ በሙሉ ሊረዱ በማይችሉበት ማህበረሰብ ውስጥ እንኳን ለርህራሄ፣ ለመቀበል እና ለማደግ ብዙ ቦታ እንዳለ አሳይተውኛል። ለዚያም ለዘላለም አመሰግናለሁ።